በያንዳንዱ የእምነት ክሬ
እንደሹራብ ተተርትሬ
እንዳልጣፍ እንዳልሰፋ ሆኛለው
የቀረኝ ጨርቅ ከቅዳጄ ያነሰ ነው ።
የሲዖል መልህቅ ከግሬ ታስሯል
እፍግ ሰንሰለቱ እሄድኩት ድረስ ይረዝማል
ቁርጭሚቴ ካልቦ ያለረፍት ይንቋቋል
ህልው ምልክቴ ጠፍረ ባርያ ሆኗል ።
* * *
ቀደም . . .በሌት ግርማ ታውሬ
ስቀይርህ ሳፈስህ ከደምስሬ
በፋኑዔል ክንፍ ሰበዝ
ደምቀለም ነክሬ ነብሴን ላውሬ ስቤዥ
ዝም ብለኸኛል !
በካሚዮን ከሚንቦገቦገው
በጥፍሮቹ ምድርን ቧጦ ከከበበው
አይሆኑ ውዬ
ለሌጊዮን ግዞት ስሸጥ በፊርማዬ
ደግመህ ዝም ብለኸኛል !
በዚ ዝምታህ
ዘላለምን ንቄ ቀቢፅ አፍታን ቃረምኩ
ባይኖር ነው ብዬ ውድ ነብሴን ገበርኩ ።
* * *
ጌታዬ
አሁን ድንገት ዞሬ
ከአፀድህ አስጠግተህ ከቀኝህ ደምረኝ
ለማለት አቅም አጣሁ የግብዝ ንሰሐ መሰለኝ
ነቀርሳዬ እንደው ስር ሰዷል
ከጥፍሬ በቀር ገላሄ ሁሉ በሀጥ ነዷል
አባት ሆይ . . .
ሱባዔ ጠፍቶብኛል ፀሎት ካደረስኩ ቆይቻለሁ
ልመና እንደማያውቅ ትኩስ ድውይ ፊትህ አለሁ
ዝምታህን ሻረው እያልኩ በዝምታ አለቅሳለሁ
ምሉእ ውስተ ኩሉ
አመድ ሳልሆን አጥንቶቼ እንዳሉ
ሥለማያልቀው የምህረትህ ፀዳል
በትላንትዬና ዛሬ መሀል
የነበረን ዝምታህን ማረኝ
አቤቱ ማረኝና ፤
አናግረኝ !